በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል በተፈጠረው ሁከት ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች የሚውሉ ድጋፎች ወደ ጅግጅጋ ተልከዋል

በትእግስት አብርሃም

አዲስ አበባ፣ ነሃሴ 3፣ 2010 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ከተሞች በተፈጠረው ሁከት ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች የሚውል አልሚ ምግብ እና ሌሎች ድጋፎች ዛሬ ወደ ጅግጅጋ መላካቸውን የብሄራዊ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን ገለፀ።

የኮሚሽኑ ኮሚሽነር አቶ ምትኩ ካሳ ከፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ጋር ባደርጉት ቆይታ፥ ዛሬ ከቀኑ ስድስት ሰአት ከድሬዳዋ የተነሳው እርዳታ ማምሻውን ጅግጅጋ እንደሚደርስ ተናግረዋል።

በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ከተሞች በተፈጠረው ሁከት በርካቶች በደረሰባቸው ጥቃት ምክንያት ቤታቸውን ጥለው በእምነት ተቋማት እና ደህንነታችን ይጠበቃል ባሉባቸው ቦታዎች ላይ ተጠልለው ይገኛሉ።

ተጎጂዎቹ እንደሚሉት በእንዲህ አይነት አስቸጋሪ ሁኔታ ሰድስት ቀናትን አስቆጥረዋል።

በእነዚህ ቀናትም የውሃ እና የምግብ እርዳታ ከመንግስት በኩል እንዳልተደረገላቸው ነው ተጎጂዎቹ ለጣቢያችን ያደረሱት የስልክ ጥሪዎች የሚገልጹት።

ከኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል የእስልምና እምነት አባቶች የተወሰነ ድጋፍ ሲደረግላቸው እንደነበር የገለጹት ተጎጂዎቹ፥ ድጋፉ ግን ከተረጂው ቁጥር ጋር ስለማይመጣጠን ለሽማግሌዎቹም ድጋፉን ማቅረብ አስቸጋሪ ሆኖባቸዋል።

ከምግብ እጥረት እና የውሃ ጥሙ በዘለለም ህጻናት እና አቅመ ደካሞች ለተለያዩ በተላላፊ በሽታዎች የከፋ ጉዳት ይደርስብናል ብለው ሰግተዋል።

የብሄራዊ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነር ምትኩ ከሳ ዛሬ ከሰዓት በኋላ እርዳታው የዘገየው በነበረው የጸጥታ ችግር ምክንያት እንደሆነ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ገልጸዋል።

በትናንትናው እለት ግን በክልሉ የተለያዩ ከተሞች ከነበሩ የኮሚሽኑ የእርዳታ መጋዘኖች የተወሰነ እርዳታ ተሰጥቷል ያሉት ኮሚሽነሩ፥ ይሁን እንጂ ይህም እርዳታ በቂ እንዳልነበር ነው የገለጹት።

ዛሬ ስድስት ሰአት ላይ ከድሬዳዋ የተነሳ እርደታ ወደ ጅግጅጋ እየሄደ መሆኑን በመግለጽ፤ እርዳታው ማምሻውን ይደርሳል ተብሎ ይጠበቃል ብለዋል።

አቶ ምትኩ እንዳሉት በጅግጅጋ ከተማ ያለው የአለም የምግብ ፕሮግራም እርዳታውን መስጠት መጀመሩን ተናግረዋል።

ከጅግጅጋ ውጪ ያሉ ከተሞችም በከተሞቹ ባለው የአለም ምግብ ፕሮግራም ማሰራጫዎች አማካኝነት እርዳታው ይደርሳቸዋል ያሉን ሲሆን፥ የነዚህ ከተሞች ድጋፍ ግን ዛሬ መድረስ ካልቻለ ከነገ ጀምሮ እንደሚሰጥ ነው የጠቆሙት።

ከዚህ በተጨማሪ ከአዳማ ከተማ ምግብ ነክ ያልህኑ የተለያዩ እርዳታዎችን የጫኑ ተሽከርካሪዎች ጉዞ የጀመሩ ሲሆን፥ በጣም ወሳኝ የሚባሉ የእርዳታ አይነቶችን ደግሞ በአውሮፐላን ለማድረስ እየተሰራ ነው።

በተለይም በጅግጅጋ፣ ቀብሪ ድሃር እና ጎዴ የአውሮፕላን ማረፊያዎች ስላሉ እነዚህን አርዳታዎች እዛ በማድረስ ከዛ ደግሞ በተሽከርካሪ ወደ ሚፈልጉበት ቦታዎች ለማገጓጓዝ እየተሰራ ነው።

አሁን ላይ ከተሞቹ እና ወደ ክልል የሚወስዱ መንገዶችም በመከላከያ ሰራዊት ቁጥጥር ስር በመሆናቸው ህብረተሰቡን በማስተባበር እርደታው በፍጥነት ለህብረተሰቡ ለማሰራጨት እየተሰራ ነው እንደ ኮሚሽነሩ።

ይህም በሁሉም አካባቢ የተጠለሉ እና ተደብቀው ያሉ እርዳታ ፈላጊዎች እስኪደርሳቸው ድረስ ይቀጥላል ብለዋል።

Editor’s Note: This article appeared first on Fana Broadcasting Corporation.

Share: