አቶ አለምሰገድ ዘውዱ ከአዲስ አበባ መገናኛ ብዙሀን ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተርነት ተሰናበቱ

የአዲስ አበባ መገናኛ ብዙሃን ኤጀንሲ በተደጋጋሚ እየቀረበበት ካለው የአመራር ብቃት ችግር ጋር ተያይዞ ዋና ዳሬክተር የነበሩት አቶ አለምሰገድ ዘውዱ ተነስተው የኢቴቪ የዜና ክፍል ኃላፊ የነበሩት ጋዜጠኛ እናትአለም መለሰ ተሾሙ፡፡

ኤጀንሲው የአዲስ ቴሌቪዥን፤የአዲስ ልሳን ጋዜጣ እና የኤፍ ኤም 96.3 በስሩ የሚገኙ ሲሆን የከተማዋ ምክርቤት የማህበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮምቴ በቅርብ ባደረገው ስብሰባ ላይ የኤጀንሲው የበላይ አመራሮች የህዝብ ፍላጎትና ችግር እንዳይነገር አፈና እንደሚያደርጉ መናገራቸው አይዘነጋም፡፡

የአዲስ አበባ መገናኛ ብዙሃን ኤጄንሲ ምክትል ስራ አስኪያጅ አቶ መብራቴ ኃይሌ በምክር ቤቱ አባላት የተሰነዘረው አስተያየት ትክክል ነው በሚል የኤጀንሲውን ድክመት በይፋ ማመናቸው የሚታወስ ነው፡፡

በተለይ የምክር ቤቱ ማህበራዊ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ አባላት አያይዘውም በኤጀንሲው የሙያ ነጻ  ባለመኖሩ ጋዜጠኞች ደመወዝ እየቀነሱ ጭምር ተቋሙን እየለቀቁ መሆኑን፣

ጋዜጠኞች ደክመው ያመጧቸውን የህዝብ ቅሬታ ዘገባዎች በአመራሮች ተቆራርጠውና ተዛብተው እንደሚቀርቡና ሳይተላለፉ እንደሚቀሩ አባላቱ መግለጻቸውን የዘገበው የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ነው።

Share: